
ባሕር ዳር: መስከረም 27/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ተከስቶ በነበረው የጸጥታ ችግር በባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ሰባታሚት ማዕከል ሥልጠና ሲወስዱ የነበሩ አንደኛ ዙር ተጠርጣሪዎች ስልጠናውን አጠናቅቀዋል።
ሥልጠናው በሰላም አስፈላጊነት፣ በግጭቱ ስለደረሰው ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳት፣ የሕግ የበላይነት፣ በሀገር የመከላከያ ሠራዊት ክብር፣ በሀገራዊ መግባባት፣ ሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነት እንዲጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች እና በቀጣይ ከማኅበረሰቡ ጋር በመቀናጀት መከናወን በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንደነበር የባሕር ዳር ማረሚያ ቤት መምሪያ ኀላፊ ምክትል ኮማንደር ተሻገር ባየ ገልጸዋል።
ኮማንደሩ እንዳሉት ሥልጠናው የተሰጠው አውቀውም ኾነ ሳያውቁ በነበረው የጸጥታ ችግር “ተሳትፈዋል” ተብለው ለተጠረጠሩ ግለሰቦች ነው።
የክልሉ ሰላም እንዲረጋገጥ፣ ልማት እንዲፋጠን፣ የመልካም አሥተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ፣ የሕዝብ ጥያቄዎች በሰላማዊ መንገድ እንዲመለሱ ከማኅበረሰቡ ጋር በመቀናጀት የድርሻቸውን እንደሚወጡም የሥልጠናው ተሳታፊዎች ገልጸዋል።
የተዘረፉ ንብረቶች እንዲመለሱና የወደሙ ተቋማት ሥራ እንዲጀምሩ ኀላፊነታቸውን እንደሚወጡም የስልጠናው ተሳታፊዎች ገልጸዋል።
ዘጋቢ:–ዳግማዊ ተሰራ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!