የታገቱ ተማሪዎች ያሉበትን ቦታ እንደሚያውቅ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ገለጸ፡፡

880

ባሕር ዳር፡- ጥር 20/2012ዓ.ም (አብመድ) የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የታገቱ ተማሪዎችን በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር እንደሻው ጣሰው፣ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ እና የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ ንጉሱ ጥላሁን ናቸው መግለጫ የሰጡት፡፡ የመግለጫው ትኩረት ደግሞ በኦሮሚያ ክልል፣ ቄሌም ወለጋ ዞን በደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ሲማሩ የነበሩ የታገቱት ተማሪዎችን የተመለከተ ነበር፡፡ በመግለጫው እንደተመላከተው ተማሪዎቹ የታገቱት ከዩኒቨርሲቲው በጋምቤላ አድርገው አዲስ አበባ ለመግባት በማይጠበቅ አቅጣጫ ሲጓዙ ነው፡፡ አንፋሎ ወረዳ ሱዲ በሚባል ቀበሌ ላይ ኅዳር 25/2012 ዓ.ም እንደተያዙም ተረጋግጧል ብለዋል በመግለጫቸው፡፡ የተማሪዎች መታገት ሪፖርት እንደተደረገም መከላከያ ሠራዊት ወደ ሥፍራው ገብቶ ከዚህ ቀደም 21 ተማሪዎች እና ተጨማሪ ሰዎችን ማስለቀቁን ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎቹ አመላክተዋል፡፡

የምርመራ ሂደቱን ያስተጓጉላል በማለት የሥራ ኃላፊዎቹ ለጊዜው የአጋቾችን ማንነት በግልጽ ከመጥራት ተቆጥበዋል፡፡ ለጊዜው ‹‹ሽፍቶች›› በሚል መጠሪያ የተገለጹት አጋቾች ከዚህ ቀደም በአካባቢው ባለሃብቶችን፣ ወጣቶችን እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችንም አግተው እንደነበር ነው የተገለጸው፡፡

ስላሉበት ሁኔታ ከወላጆች እና ከሕዝቡ በመንግሥት ግልጽ ማብራሪያ እንዲሰጥ የተጠየቀባቸው 17 ተማሪዎችን በተመለከተም ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ከዩኒቨርሲቲው የመረጃ ቋት እና ከሀገር አቀፍ የፈተናና ምዘናዎች ኤጀንሲ ተደረገ በተባለው ማጣራት 12ቱ የደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቱ ተማሪዎች ናቸው፤ አምስቱ ግን የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች እንዳልሆኑ ነው የተገለጸው፡፡ አምስቱ ታጋቾች ታዲያ የአካባቢው ነዋሪዎች ይሁኑ ወይም ከሌላ ቦታ የመጡ ስለመሆናቸው በመግለጫው አልተብራራም፡፡

ከ17 በተጨማሪ ሁለት ቤተሰቦች ‹ልጆቻችን ጠፍተዋል› በማለት ሪፖርት ማድረጋቸውን ተከትሎ በተደረገ ማጣራት ሁለቱም የደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መሆናቸው ተረጋግጠዋል ነው ያሉት የሥራ ኃላፊዎቹ በመግለጫቸው፡፡ በዚህም መሠረት አድራሻቸው ያልታወቁት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎቸ 14 ይሆናሉ፡፡ እነዚህ እና አምስቱን ጨምሮ 19 ሰዎች የት እንዳሉ፤ ማን፣ እንዴትና ለምን እንዳገታቸው ምርመራ እየተደረገ ነው፡፡ ለዚህም አንድ የምርመራ ቡድን ተቋቁሞ እየሠራ መሆኑን ነው የገለጹት፡፡

የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር እንዳሻው ጣሰው እንደገለጹት ደግሞ የታገቱ ተማሪዎች ያሉበትን ቦታ በተመለከተ ፖሊስ መረጃው አለው፤ ክትትልም እየተደረገ ነው፡፡ ‹ጉዳት ደርሶባቸዋል› የተባለውን መረጃ በተመለከተ ግን እስካሁን በፖሊስ የተደረሰበት መረጃ እንደሌለ ነው ያስታወቁት፡፡ ጉዳዩ ውስብስብና ጥንቃቄ የሚጠይቅ በመሆኑ በአካባቢው ኢንተርኔትና ሥልክ መቋረጡመንም ገልጸዋል፡፡ በመግለጫው እንደተመላከተው እስካሁን 800 የደምቢዶሎ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው አንዳቋረጡ አልተመለሱም፡

ዘጋቢ፡- ጋሻው ፈንታሁን

ፎቶ፡- ከፋብኮ

Previous articleቻይና 1 ሽህ አልጋዎች ያሉት ሆስፒታል በ48 ሰዓታት ገንብታ ሥራ አስጀመረች፡፡
Next articleዐይነ ሥውሩ የፈረስ ጉግስ ውድድር አሸናፊ!