
ደሴ፡ መስከረም 16/2016 ዓ.ም (አሚኮ) የነብዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) የመውሊድ በዓል በኮምቦልቻ ከተማ 08 ቀበሌ በሚገኘው መጂት መስጅድ ነው እየተከበረ የሚገኘው።
በመስጅዱ የመውሊድ በዓልን ለመታደም ከተለያዩ አካባቢዎች በርካታ አማኞች ይገኛሉ።
1ሺህ 498ኛው የነብዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) የልደት (የመውሊድ) በዓልም ከመስከረም 15/2016 ዓ.ም ጀምሮ እየተከበረ ይገኛል።
በመስጅዱ የመውሊድ በዓል በየዓመቱ በድምቀት የሚከበር ስለመኾኑ በበዓሉ ላይ የተገኙ አሚኮ ያነጋገራቸው አማኞች ተናግረዋል።
የመውሊድ በዓል በመጂት መስጅድ ሲከበር መተባበርና መተጋገዝ በሰፊው የሚታይበት መኾኑን የሚገልጹት ተሳታፊዎቹ የአካባቢው ማኅበረሰብ ሃብቱንና ጉልበቱን ሳይሰስት የሚሳተፍበት መኾኑንም ገልጸዋል።
በዓሉ ሲከበር በመስጅዱ ለተገኙት አማኞች የዳዕዋ ፕሮግራም እንደሚከናወንም ነው የበዓሉ ታዳሚዎች የነገሩን
ዘጋቢ፦ ተመስገን አሰፋ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!