
ባሕርዳር፡ መስከረም 15/2016 ዓ.ም (አሚኮ) ከ360 በላይ የሚኾኑ የቀድሞ መከላከያ ሠራዊትና ተመላሽ የሰራዊት አባላትን የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ ተጠቃሚ ለማድረግ እየሠራ መኾኑን የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር ኅብረት ሥራ ተጠሪ ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።
የጽሕፈት ቤቱ አደራጅ ባለሙያ አቶ አሰፋ አሳምነው የሀገር ባለውለታ የኾኑት የቀድሞ የመከላከያ ሠራዊት በማኅበር ተደራጅተው ቦታ እንዲያገኙ ለማድረግ ምዝገባ እየተካሄደ ነው ብለዋል። ከነሐሴ 21/2015 ዓ.ም ጀምሮ ከ360 በላይ የሠራዊቱ አባላት መመዝገባቸውንም ተናግረዋል። መረጃ በማጣራት ሂደት ምክንያት ምዝገባው መዘግየቱን ገልጸው አሁንም በሠራዊት አባላቱ ጥያቄ መሰረት እስከ መስከረም 18/2016 ዓ.ም ድረስ ተራዝሟል ብለዋል።
በምዝገባው መስፈርቱን የሚያሟሉ ሁሉም የከተማው ነዋሪ የቀድሞ መከላከያ ሠራዊት እኩል ተጠቃሚ ናቸው ብለዋል። በ2010 ዓ.ም በርከት ያለ ቁጥር ያላቸው ተመላሽ ሠራዊት በ12 ማኅበራት ተደራጅተው ቦታ ማግኘታቸውንም አስታውሰዋል።
ተቋሙ ሕግ እና መመሪያው በሚፈቅደው መሰረት ተጠቃሚዎችን በአገልግሎት ለማርካት በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝም አቶ ተስፋ ተናግረዋል።
ዘጋቢ፦ ወንድይፍራ ዘውዴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!