ከ1 ነጥብ 6 ሚሊየን በላይ ለሆኑ ሰዎች ሕክምና የሚውል የወባ መድኃኒት ተሠራጨ።

51

ባሕር ዳር: መስከረም 11/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ከ1 ነጥብ 6 ሚሊየን በላይ ሰዎችን ሊያክም የሚችል የወባ መድኃኒት ባለፉት ሦስት ወራት መሠራጨቱን የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት አስታወቀ፡፡

እንዲሁም ከ1 ነጥብ 6 ሚሊየን በላይ ሰዎችን ሊያክም የሚችል መድኃኒት በክምችት መኖሩን የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሰሎሞን ንጉሴ ለፋብኮ ተናግረዋል፡፡

በዚህ ዓመት ባልተለመደ ሁኔታ የወባ ወረርሽኝ መከሰት የመድኃኒት ክምችት መጠኑን እንዳሳሳው አንስተው የመድኃኒት ስርጭቱ ቀድሞ ከነበረው ከሦስት ዕጥፍ በላይ ጨምሯል ብለዋል፡፡

የግዥ ሂደቱን በማፋጠን የመድኃኒት አቅርቦቱ ሳይቆራረጥ እንዲቀርብ እየተደረገ ስለመሆኑም ጠቁመዋል፡፡

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የታካሚዎች ቁጥር ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት አቶ ሰሎሞን በጅማ ቅርንጫፍ በኩል በቂ መድኃኒት ስለተሰራጨ የአቅርቦት ዕጥረት አለመኖሩን አስረድተዋል፡፡

በሌላ በኩል በአማራ ክልል በተፈጠረው የፀጥታ ችግር ምክንያት በክልሉ የሚገኙ ቅርንጫፎች መድኃኒቱን በንቃት ለጤና ተቋማት እያደረሱ ባለመሆናቸው የአቅርቦት መቆራረጥ ተከስቷል ነው ያሉት፡፡

ይሁን እንጂ ባሕር ዳር፣ ጎንደር እና ደሴ ለሚገኙ ቅርንጫፎች በአውሮፕላን ጭምር መድኃኒት ለማድረስ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ነው ያረጋገጡት፡፡

በሀገር አቀፍ ደረጃ የወባ መድኃኒት ዕጥረት ባይኖርም ሰው ሠራሽ ዕጥረቶች ግን ፈተና ሆነውብናል ብለዋል፡፡

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleበቀሪ ቀናት በሚካሄደው የተማሪዎች ምዝገባ ማኅበረሰቡ የድርሻውን እንዲወጣ የምዕራብ ጎንደር ዞን ትምህርት መምሪያ ጥሪ አቀረበ።
Next articleየጥላቻ ንግግር ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ ምስቅልቅሎችን እያስከተለ ነው።