
ባሕር ዳር: መስከረም 10/2016 ዓ.ም (አሚኮ)ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ በኒውዮርክ ባሰሙት ንግግር ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐግብሯ አማካይነት አመርቂ ሥራ በማከናወን ላይ መሆኗን ገልፀዋል። ላለፉት 5 ዓመታት በተከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐግብር ከ32 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን ጠቅሰዋል። ሀገሪቱ እንደየአደጋው ስፋት፣ ጥልቀት እና ድግግሞሽ ተለዋዋጭ የኾነ የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቅ ሥርዓት እንደምትከተልም አብራርተዋል።
በተመድ ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ የተጀመረውን እና “የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥርዓት ለሁሉም” የተሰኘውን ኢኒሼቲቭ ያደነቁት አቶ ደመቀ፤ ለተግባራዊነቱ የተቀናጀ ትብብር እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል። በሀገር አቀፍ፣ በአህጉር አቀፍ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ብቁ እና ውጤታማ የኾነ የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥርዓት ለመዘርጋት የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የገንዘብ ድጋፍም ወሳኝ መኾኑንም መናገራቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!