
ባሕር ዳር: ጳጉሜን 03/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ጳጉሜን 3 የበጎነት ቀን “በጎነት ለሀገር” በሚል መሪ መልዕክት እየተከበረ ነው።
በአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የዳዕዋና የትምህርት ዘርፍ ኀላፊ ሸህ ሙሐመድ ኢብራሂም በቁራን ከተገለጹት መርኾች በጎነት በሦስተኛ ደረጃ እንደተቀመጠ ተናግረዋል። በጎነት ብዙ ሃሳቦችን ጠቅልሎ የያዘ እንደኾነም ያነሳሉ። በጎነት በገንዘብ፣ በጉልበት በሙያ፣ በአስተሳሰብ ሊገለጽ ይችላልም ብለዋል።
በጎ ለመሥራት እድሜ፣ ጾታ፣ የጤና ሁኔታ፣ የሃብት ደረጃ አይወስነውም ያሉት ሸህ ሙሐመድ ሰው ለሰው፣ ሰው ለእንስሳት፣ ሰው ለእፅዋት በጎ ያደርጋል ብለዋል። በጎ የሚለው ሀሳብ ሰፊ ማኅደር አለው ያሉት ሸህ ሙሐመድ በጎ መሥራት ለሰውም ለሀገርም ጠቃሚ እንደኾነ አስረድተዋል።
በጎነት ከሰዎች ጋር ያዛምዳል ፣ከፈጣሪ ጋር ያስታርቃል፣ ማንነትን ይገልጻል ነው ያሉት።
በእስልምና ሃይማኖት አስተምህሮ በጎነት በዘር፣ በሃይማኖት፣ በጊዜ አይገደብም ብለዋል። በጎነት ኹሉም በሚችለው አቅሙ ሊሠራው የሚችል ዋጋ የሚያሠጥ ነው ሲሉም ሃሳባቸውን ለአሚኮ አጋርተዋል።
ዘጋቢ:- ትርንጎ ይፍሩ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!