
አዲስ አበባ: ነሐሴ 30/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ጉባኤው በጳጉሜ ቀናት የሚከናወኑ መንፈሳዊ ተግባራትን አስመልክቶ የጋራ መግለጫ ይፋ አድርገዋል።
መግለጫውን የሰጡት የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የበላይ ጠባቂ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ታጋይ ሲኾኑ ባለፋት ዓመታት በብዙ መንገድ ፈጣሪን አስቀይመናል ፤ በደላችንን ይቅር ይለን ዘንድ በፆምና በጸሎት ልንጠይቀው ይገባል ብለዋል።
በሀገራችን የተፈጠሩ እና እተፈጠሩ ያሉ ውስብሰብ ችግሮች በጥንቃቄና በጥበብ መፍታት ካልተቻለ ግፍና መከራ እናጭዳለን ብለዋል።
ያሉ እና የነበሩ ስብራቶች መጠገን የሚቻለው በጸሎትና ንስሓ እንዲሁም በይቅርታ በመኾኑ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደዬ እምነቱ የጳጉሜ ቀናትን በጸሎት ፣ በንስሓ እንዲሁም ይቅርታ ማሳለፍ ይገባል ብለዋል። ይሄን በማድረግ አዲሱን 2016 ዓ.ም በሰላም ልንቀበል ይገባል ብለዋል።
ጸሎት ፣ ንስሓና ፍቅር የመርሐ ግብሩ ዋና ዓላማዎች እንደኾኑም ተገልጿል። እያንዳንዱ የሃይማኖት ተቋማት ከጳጉሜ አንድ ጀምሮ እስከ አምስት እንደ ሥርዓታቸው ከአምላካቸው ጋር የሚገናኙበትን መርሐ ግብር መዘጋጀታቸውንም ገልጸዋል።
ጳጉሜ 5 ከቀኑ 7:00 ጀምሮ ደግሞ ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት በወዳጅነት አደባባይ ተገኝተውም መልዕክት ያስተላልፋሉ ተብሏል።
ዘጋቢ:- በለጠ ታረቀኝ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!