
አዲስ አበባ: ነሐሴ 25/2015 ዓ.ም (አሚኮ)የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ከበደ ደሲሳ የጳጉሜን ስያሜዎች እና አከባበራቸዉን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም ኢትዮጵያ በዓመቱ የሰሜኑን ጦርነት በሰላማዊ ዉይይት መፍታት መቻሏ እና የስንዴ ምርትንም ወደ ዉጭ መላክ መጀመሯ ስኬቶች ናቸዉ ብለዋል።
ኢትዮጵያ ብሪክስን መቀላቀል መቻሏ በዓመቱ ያሳየችዉ የዲፕሎማሲ ስኬት እንደኾነም አስረድተዋል።
በዚህ ዓመት የኑሮ ዉድነት እና በየአካባቢዉ የሚፈጠሩ ግጭቶች ፈተና እንደነበሩም ነው ያስገነዘቡት።
የጳጉሜን ቀናት አከባበርን አስመልክቶ ሚኒስትር ዴኤታው እንዳሉት፡-
✍️ጳጉሜን 1 የአገልግሎት ቀን ተብሎ ተሰይሟል ፤በዚህ ቀን ሀገር እና ሕዝብን ማገልገል ምን ማለት እንደኾነ ግንዛቤ የሚሰጥ እና ለተሳታፊዎች ምሥጋና የሚቀርብበት ነው፡፡
✍️ ጳጉሜን 2 የመሥዋዕትነት ቀን ነው ፣በዚህ ቀን የጸጥታ አካላት ሥራ የሚታይበት ፤መሥዋዕትነት የከፈሉ ዜጎች የሚወሱበት ቀን ተብሎ ተሰይሟል።
✍️ጳጉሜን 3 የበጎነት ቀን ሲኾን በጎ አድራጎት ያለዉ አስተዋጽኦ ይወሳበታል፡፡
✍️ጳጉሜን 4 የአምራችነት ቀን ነው ፤ በዚህ ቀን በሀገራቸዉ ሀብት ያፈሩ አካላት ይመሠገኑበታል፡፡
✍️ጳጉሜን 5 የትዉልድ ቀን ተብሎ የተሰየመ ሲኾን ታዳጊዉ ትዉልድ የሚረከባትን ሀገር የሚዘክርበት ቀን ነዉ።
✍️ጳጉሜን 6 የአብሮነት ቀን ተብሎ የሚዘከር መኾኑን ሚኒስትር ዴኤታዉ ከበደ ዴሲሳ ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡- ኤልሳ ጉዑሽ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!