
ባሕር ዳር: ነሐሴ 22/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ በ73ኛው የአፍሪካ አሕጉር የዓለም ጤና ድርጅት መድረክ ላይ እየተሳተፈ ነው።
በመድረኩ ከ20 በላይ በሚሆኑ የተለያዩ የጤና አጀንዳዎች ላይ ውይይት እንደሚደረግ የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡
የአፍሪካ ማኅበረሰብ ጤና አኹናዊና ቀጣይ ስትራቴጂክ ጉዳዮች ከዓለም ማኅበረሰብ ጤና ጋር ያላቸው አጠቃላይ ኹኔታም በመድረኩ ይዳሰሳል ተብሏል፡፡
ከዚህ ባለፈም አራት የመፍትሄ ሃሳቦችን የያዙ ሰነዶች ቀርበው በአባል ሀገራቱ እንደሚጸድቁ ይጠበቃል።
ኢትዮጵያ የተለያዩ መግለጫዎችን በመድረኩ የምታቀርብ ይኾናል። በጎንዮሽ መድረክም ልዑካኑ እንደሚሳተፉ ተጠቁሟል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!