
ባሕር ዳር፡ ታኅሳስ 20/2012ዓ.ም (አብመድ) የሠላም ሚኒስቴር የዜጎችን ደኅንነትና ብሔራዊ ጥቅሞች ለማስከበር፣ በሚከሰቱ ማኅበራዊ ችግሮችና ግጭቶች ምክንያት የተዛቡ ግንኙነቶች ወደ ቀደመው ለመመለስ የሚያስችሉ የተለያዩ የሠላም ግንባታና ብሔራዊ መግባባት ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አንድነቷ የተጠናከረ፣ ማኅበራዊ መስተጋብሯ የተሟላና ሠላሟ የተጠበቀ ኢትዮጵያ እንድትኖር በሚደረገው አገራዊ ተልዕኮ ቀዳሚ ሚናውን ለመወጣት ሰፊ እንቅስቃሴዎች እየደረገ መሆኑንም አመላክቷል፡፡
እነዚህን ተግባባራት ለማሣካትም ለብሔራዊ አንድነትና ዘላቂ ሠላም መከበር የማይተካ ሚና ያላቸውን የማኅበረሰብ ክፍሎች በማቀራረብ እንዲወያዩና ለሀገር ግንባታ የሚጠቅሙ ሐሳቦች እንዲሸራሸሩ መድረኮችን የማመቻቸት ሥራዎችን እየሠራ እንደሆነም የሠላም ሚኒስቴር በማኅበራዊ ገጹ ገልጿል፡፡
ሚኒስቴሩ ከ‹ጀስቲስ ፎር ኦል ፕሪዝን ፌሎው ሽፕ› ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ከሶማሌና ከአፋር ክልሎች የተወጣጡ የሀገር ሽማግሌዎች የምክክር መድረክ ነገ ታኅሣሥ 21 ቀን 2012 ዓ.ም በአዳማ ከተማ እንደሚያካሂድ አስታውቋል፡፡