
ወልድያ: ሐምሌ 20/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የጋዞ ወረዳ አሥተዳዳሪ ተመስገን ፍቃዴ በወረዳው በረዶና ነፋስ ቀላቅሎ የጣለው ዝናብ ያደረሰው የጉዳት መጠን እየተለየ መኾኑን ገልጸዋል፡፡
👉 መረጃው እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስም ከ150 በላይ የመኖሪያ ቤቶች በእስታይሽና ዙሪያው ቀበሌዎች ውድመት መድረሱን ነው አቶ ተመስገን ለአሚኮ የተናገሩት።
የጉዳት መጠኑ ሊጨምር እንደሚችል የተናገሩት አሥተዳዳሪው የደረሰው ጉዳት በወረዳው አቅም የሚመለስ አይደለም ብለዋል።
👉 ሐምሌ 19/2015 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ በጣለው ከፍተኛ ነፋስና በረዶ የቀላቀለ ዝናብ አብዛኞቹ አቅመ ደካማ አረጋዊያን እና በሥራና ሥልጠና የተደራጁ ወጣቶች የጉዳቱ ሰለባ መኾናቸውን አስረድተዋል፡፡
👉 ጉዳቱ ከእስታይሽ ከተማ በተጨማሪ በሌሎች ቀበሌዎችም ከ350 ሄክታር በላይ መሬት የበልግና የመኸር ሰብል ላይ ጉዳት ደርሷል።
👉 ግለሰቦች፣ ረጅ አካላትና በየደረጀው ያለው የመንግሥት አካል ለዕለት የመጠለያ እና የምግብ ድጋፍ እንዲያደርጉ አሥተዳዳሪው ጥሪ አቅርበዋል።
ዘጋቢ፡- ባለ ዓለምየ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!