
ባሕር ዳር: ሐምሌ 19/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ሰሜን ምዕራብ ዕዝ የተሰጠውን ተልዕኮ በላቀ ጀግንነት የፈፀመና በርካታ ጀግኖችን ያፈራ ታሪክ ሠሪ ዕዝ መሆኑን የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ።
የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በዕዙ ዓመታዊ የሥራ አፈፃፀም ውይይት ማጠቃለያ ላይ ተገኝተው እንደተናገሩት ሰሜን ምዕራብ ዕዝ በአስቸጋሪ የፖለቲካ ሁኔታ ውስጥ ለውጥ የወለደው የመከላከያ ቀኝ እጅ ነው ብለዋል።
ሁሌም በሚፈፅመው ተልዕኮ የሚያኮራ ዕዝ መሆኑንም አስታውቀዋል።
“እንደ ዕዝ የተሰጣችሁ ተልዕኮ ኢትዮጵያን ማቆየትና ማሻገር ነው ለዚህም ሠራዊቱን በሥነ-ልቦናና በወታደራዊ ሳይንስና ጥበብ ማብቃት ይጠበቅባችኋል” ያሉት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ተልዕኳችሁንም በገለልተኝነት፣ ስብዕናን በመላበስ፣ ዲሲፕሊን በማክበርና በውጤታማነት በመፈፀም የፕሮፌሽናል ሠራዊት ባህሪን መላበስ ይገባል ብለዋል።
በዕለቱም የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላና የዕዙ አመራሮች በጠቅላይ መምሪያው ቅጥር ግቢ ችግኝ በመትከል የአረንጓዴ አሻራቸውን ማኖራቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!