
ባሕር ዳር: ሐምሌ 17/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በምስራቅ ጎጃም ዞን ሰዴ ወረዳ 4 ቀበሌዎችን የሚያገናኘው ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የተገነባው የተፌ ወንዝ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።
በአማራ ክልል መንገድ ቢሮ ወጭ የተገነባው የተፌ ወንዝ 24 ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን 20 ሚሊዮን 900 ሽህ ብር ወጭ ተደርጎበታል።
ድልድዩ በአካባቢው ለሚገኙ የ4 ቀበሌ ነዋሪዎች አገልግሎት እንደሚሰጥ ከወረዳው መንገድና ትራንስፖርት ጽሕፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
ግንባታው ተጠናቅቆ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የተፌ ወንዝ ድልድይ የአካባቢ ሕዝብ የረጅም ዓመት የይገንባልኝ ጥያቄ እንደነበርና የድልድዩ መገንባት ማኅበረሰቡ የሚያመርተውን የግብርና ምርት ወደ ገበያ ለማቅረብ ብሎም ሌሎች አገልግሎቶችን ለማግኘት ፋይዳው የጎላ ነው ተብሏል።
ለአገልግሎት ክፍት የሆነው ድልድይ የአካባቢውን ሕዝብ የረጅም ዓመት ጥያቄ መልስ የሰጡ ከመሆኑም ባሻገር የማኅበረሰቡን እንግልትና ሲቃይ እንደሚያቃልል በምረቃው ወቅት ተገልጿል።
በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ የሥራ ኀላፊዎችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!