
ወልድያ: ሐምሌ 05/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በ15ተኛው የክልል ክለቦች እግር ኳስ ሻምፒዮና ዛሬ በግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ተከናውኗል።
ረፋድ 3:00 ሰዓት ላይ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ እና ቆቦ ከነማ የተጫወቱ ሲሆን በውጤቱም ቆቦ 2 ለ 1 በማሸነፍ ወደ ዋንጫ ጨዋታ አልፏል። ይህ ጨዋታ ከተጠናቀቀ በኋላ የደብረ ታቦር ተጫዋቾች በመሃል ዳኛው ላይ ቅሬታቸውን ሲገልፁና የሁለቱ ቡድን ተጫዋቾችም ለጠብ ሲጋበዙ ተስተውሏል።
ቀጥሎ የተደረገው ጣና ክፍለ ከተማን ከሙጃ ከነማ ያገናኘው መርሃግብር ነው። እንደ ቀዳሚው ጨዋታ ሁሉ በተጋጣሚ ቡድኖቹ መካከል ብርቱ ፉክክር ተደርጎ ጣና ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ 1 ለባዶ በመርታት የዋንጫ ተፋላሚነቱን አረጋግጧል። ጣና ክፍለ ከተማ የባሕር ዳር ከተማ ክለቦች ሻምፒዮን በመሆን ወደዚህ ውድድር መምጣቱ ይታወሳል።
ነገ ረቡዕ የሻምፒዮናው ማጠቃለያ ሁለት ጨዋታዎች ሲደረጉ :-
ደብረ ታቦር ዩኒቨርስቲ ከሙጃ ከነማ ጋር ጠዋት ለደረጃ ፣ ከሰዓት በኋላ ቆቦ ከተማ እና ጣና ክፍለ ከተማ የዋንጫ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የአማራ ክልል ክለቦች ውድድር ሐምሌ 5/2015 ይጠናቀቃል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!