
ባሕር ዳር: ሐምሌ 05/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በክልሉ ያለውን የበጋ መስኖ ልማትና የመኸር እርሻ ዝግጅትን በተመለከተ ቢሮው ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡
እንደ ቢሮው ማብራሪያ ፡-
. በክልሉ 278 ሺህ ሄክታር መሬት በአንደኛና ሁለተኛ ዙር አጠቃላይ በመስኖ ለምቷል፡፡ እስከ አሁንም 22 ሚሊዮን ኩንታል ተሰብስቧል፡፡ ይህም ለመሰብሰብ ከታቀደው ምርት 67 በመቶ ይሸፍናል፡፡ የምርት ስብሰባ ሂደቱም እንደቀጠለ መኾኑን ግብርና ቢሮ ገልጿል፡፡
•ከ213 ሺህ 800 በላይ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ለምቷል፡፡ ከዚህ ውስጥ እስከ አኹን 98 በመቶ ሄክታሩ በመሰብሰብ 7 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ምርት ተገኝቷል፡፡ ይህም ከባለፈው ዓመት ከነበረው በአምስት እጥፍ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል፡፡
በ2015/16 የምርት ዘመን ደግሞ በክልሉ፡-
•5 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዷል፡፡
• 160 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎም ይጠበቃል፡፡
•በዘር ለመሸፈን ከታቀደው ውስጥ እስከ አኹን 96 በመቶ አንደኛ እና ሁለተኛ ዙር እርሻ ታርሷል፡፡
• 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ደግሞ በዘር ተሸፍኗል፡፡
•ከዚህ ውስጥ ደግሞ 1 ሚሊዮን ሄክታሩ በመስመር ተዘርቷል፡፡
•ከ471 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በትራክተር ታርሷል፡፡ ለዚህም 1 ሺህ 524 ትራክተሮች ጥቅም ላይ ማዋል ተችሏል፡፡
•ምርታማነቱን በሄክታር ከ29 ኩንታል ወደ 32 ኩንታል ለማሳደግ ታቅዷል፡፡
የክልሉን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ከሚያግዙ አሠራሮች አንዱ የኩታ ገጠም እርሻ ነው፡፡ በክልሉ በዘር ለመሸፈን ከታቀደው መሬት ውስጥ 2 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በ10 የሰብል ዓይነቶች በኩታ ገጠም ለማረስ ታቅዷል፡፡ በዚህም 80 ሚሊዮን ኩንታል ወይንም የእቅዱን 50 በመቶ ምርት ለማግኘት እየተሠራ ነው፡፡ እስከ አሁንም 400 ሺህ ሄክታር መሬት በኩታገጠም በዘር መሸፈኑን የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኀላፊ ኃይለማርያም ከፍያለው (ዶ.ር) ገልጸዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ዳግማዊ ተሠራ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!