
አዲሰ አበባ: ሐምሌ 05/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ከ308 የአሠሪና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀንሲዎች ውስጥ የ109 ኤጀንሲዎች የሥራ ፈቃድ መሰረዙን የአዲስ አበባ የሥራ ኢንተርፕራይዝና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታውቋል፡፡
እርምጃው የተወሰደባቸው ኤጀንሲዎችም በሀገር ውስጥ ሠራተኞችን በማገናኘት የሚሠሩ መኾናቸውን የአዲስ አበባ የሥራ ኢንተርፕራይዝና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ የሥራ እድል ፈጠራና የምግብ ዋስትና ዘርፍ ምክትል ኀላፊ ፍስሀ ጥበቡ ናቸው፡፡
ምክትል ኀላፊው ዛሬ በሰጡት መግለጫ፤ ከኤጀንሲዎች የሥራ ስምሪት ጋር በተያያዘ ከኅብረተሰቡ ቅሬታ ሲቀርብ መቆየቱንም ተናግረዋል።
ቢሮው ቅሬታውን መሰረት በማድረግ ሰፊ የክትትል ሥራ ማከናወኑን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም ሕጋዊ አሠራር ሂደቶችን በመጣስ ሲሠሩ የነበሩ 109 የአሠሪና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀንሲዎች የሥራ ፈቃድ እንዲሰረዝ ተደርጓል ነው ያሉት።
ኤጀንሲዎች ፈቃዳቸው እንዲሰርዝ ምክንያት የኾነው፦
👉የንግድ ፈቃዳቸውን አለማደስ
👉የሠራተኛ መብት አለማክበርና
👉ውላቸውን ባለመፈጸማቸ መኾኑን ጠቅሰዋል፡፡
የመንግሥትም ኾነ የግል ቀጣሪ ተቋማት ሠራተኞችን ከኤጀንሲዎች በሚቀጥሩበት ወቅት አስፈላጊውን ማጣራት እንዲያደርጉ አሳስበዋል። በቀጣይም የሠራተኞችን መብት ለማስጠበቅ በቂ ቁጥጥሮችን እንደሚያደርጉም በመግለጫቸው አስታውቀዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ራሄል ደምሰው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!