
ደሴ: ሐምሌ 03/2015 ዓ.ም (አሚኮ)በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር አምባሳደር ሐሰን አብዱልቃድር የተመራ ልዑካን ቡድን የመጀመሪያውን የመስክ ምልከታውን በደቡብ ወሎ ዞን በአርጎባ ልዩ ወረዳ አድርጓል።
ቡድኑ በተፋሰስ ልማት የለማውን የደለመኔ ተፈሰስን በመጎብኘት የአረንጓዴ አሻራውን አሳርፏል።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ.ር) ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ማብራሪያ ላይ ለተከታታይ አስር ቀናት ሁሉም ሚኒስትሮችና ሚኒስትር ዴኤታዎች በተመደቡበት በመሰማራት የሥራ ግምገማ ያደርጋሉ ማለታቸው ይታወሳል፡፡ ይህን መሰረት በማድረግ አምባሳደር ሀሰን አብዱልቃድርም የመስክ ጉብኝቱ ዋና አላማ ሥራዎችን መሬት ላይ በመውረድ በአካል ጎብኝቶ ድጋፍ ለማድረግ ነው ብለዋል ።
በአርጎባ ልዩ ወረዳ ያየነው የተፋሰስ ልማት ለሌሎች አካባቢወዎች ልዩ ተሞክሮ የሚኾን ነው ያሉት አምባሳደሩ ኀብረተሰቡ የሚያነሳውን የውኃ ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የሚመለከተው አካል ጋር በመነጋገር ዘላቂ መፍትሔ እንሰጣለን ብለዋል።
በመስክ ጉብኝቱ ላይ የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ አስተባባሪ ሚኒስቴር ዴኤታ አቶ ሙሳ አህመድ፣ የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞን ጨምሮ ሌሎች የፌደራል ከፍተኛ የመንግስት ሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የልኡካን ቡድኑ በደለመኔ ተፋሰስ አረንጓዴ አሻራውን ያስቀመጠ ሲኾን በቀጣይ አስር ቀናትም በደቡብ ወሎ ዞን የተለያዩ አከባቢዎች ድጋፍ እና ክትትል እንደሚያደርግ ተገልጿል።
ዘጋቢ፡- አበሻ አንለይ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!