ባሕር ዳር: ሰኔ 29/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በየሦስት ወሩ ከሚታተመው “ዲፕሎማሲያችን” መጽሔት ጋር ባደረጉት ቆይታ ሀገራችን በየደረጃው ያጋጠሟትን ፈተናዎች ተሻግራ ብሔራዊ ጥቅሟን በብቃት አስጠብቃለች ብለዋል።
አቶ ደመቀ በቃለምልልሳቸው በተለያዩ ጉዳዮች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እየተከናወኑ ያሉ የለውጥ እና ተቋማዊ ማሻሻያዎች እንዲሁም ባለፉት ሁለት ዓመታት ከዲፕሎማሲ አኳያ ሀገሪቱ ገጥሟት ስለነበረው ጫና እና መንግሥት ስለወሰዳቸው ብልሃት የተሞላባቸው እርምጃዎች ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የኢትዮጵያ የግዛት አንድነት፣ ሀገራዊ ጥቅም እና ሉዐላዊ አንድነት እንዲጠበቅ መንግሥት ከሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ጋር በመኾን የተሻገራቸው በርካታ የዲፕሎማሲ ድሎችን በተመለከተ ገለፃ አድርገዋል። በተለይ ዓለም አቀፋዊ ጫናን በመቋቋም አሁን ለምንገኝበት ሰላም እና ሀገራዊ አንድነት በየደረጃው ያጋጠሙንን ፈተናዎች ተሻግረን የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ ችለናል ማለታቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!