
ባሕር ዳር: ሰኔ 20/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢፌዴሪ ትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን ለመውጫ ፈተና ለተማሪዎች አስፈላጊውን መረጃ ያላደረሱ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ዝግጅታቸውን በፍጥነት እንዲያጠናቅቁ አሳስቧል፡፡
ባለስልጣኑ ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ የመጀመሪያ ዲግሪ የመውጫ ፈተና ከሐምሌ 3 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ለመስጠት ዝግጅት መደረጉን አስታውሷል፡፡
ይሁን እንጂ ለተማሪዎቻቸው በቂ መረጃ ያላደረሱ እና የትና መቼ እንደሚፈተኑ ያላሳወቁ አንዳንድ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መኖራቸው በክትትል መረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ከዚህ ባለፈም ተቋማቱ ተማሪዎቻቸው ከሚፈተኑባቸው የመንግሥት ተቋማት ሥራ ኃላፊዎች ጋር አለመወያየት እና ሌሎች ጉድለቶች እንዳሉባቸው ተገልጿል፡፡
ስለሆነም ተቋማቱ ያሉባቸውን ክፍተቶች በአጭር ጊዜ እንዲያርሙ እና ዝግጅታቸውን እንዲያጠናቅቁ ባለስልጣኑ አሳስቧል፡፡
ተማሪዎች መረጃ ባለማግኘት ለሚደርስባቸው እንግልትና ለሚከሰተው ችግር ኃላፊነቱ የተቋማቱ መሆኑንም አስገንዝቧል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!