
አዲስ አበባ: ሰኔ 16/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ፀደይ ባንክ ከአሜሪካን ኮሌጅ ኦፍ ቴክኖሎጂ ጋር በጋራ ለመሥራት የሚያስችለዉን ስምምነት ፈጽሟል።
የጸደይ ባንክ ዋና ሥራ አሥፈጻሚ መኮንን የለዉምወሰን የተደረገዉ ስምምነት ኢንተርፕራይዞችን ለመደገፍ የሚያስችል እንደኾነ ተናግረዋል።
ዋና ሥራ አስፈጻሚው ኢንተርፕራይዞች በሀገር እድገት እና ልማት ላይ ያላቸዉ ድርሻ ከፍተኛ በመኾኑ በፋይናንስ ሊደገፉ እንደሚገባ ነው ያስገነዘቡት።
በተለይም ወጣቶች በሥራ ፈጠራ ስኬታማ እንዲኾኑ እየሠሩ እንደሚገኙ የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚዉ ባንኩ ወደ ባንክነት ከማደጉ በፊትም ሥራ ፈጣሪዎችን ሲደግፍ ቆይቷል ብለዋል፡፡ ይህንንም ለማስቀጠል እንደሚሠሩ ነው ያብራሩት፡፡
የአሜሪካን ኮሌጅ ኦፍ ቴክኖሎጂ ፕሬዚዳንት አስማማዉ አጥናፉ (ዶ.ር) “አዳዲስ ሥራ ፈጣሪዎችን ለማፍራት በሚደረገዉ ጥረት በጋራ እንሠራለን” ብለዋል።
ዶክተር አስማማዉ ኢንተርፕራይዞችን በፋይናንስ በመደገፍ እና ለሠራተኞች ሥልጠና በመስጠት በጋራ እንደሚሠራም አስገንዝበዋል።
ዘጋቢ፡- ኤልሳ ጉኡሽ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!