
ባሕር ዳር: ሰኔ 10/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ርስቱ ይርዳው በዛሬው እለት አዲሱን የዓባይ ወንዝ ድልድይ ግንባታ ሒደትን ተመልክተዋል።
በ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በጀት እየተገነባ የሚገኘው አዲሱ የዓባይ ወንዝ ድልድይ ግንባታ የማጠናቀቂያ ሥራዎች እየተፋጠኑ እንደሚገኝ በጉብኝቱ የተገለጸ ሲሆን ግንባታው ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ በነባሩ የዓባይ ወንዝ ድልድይ ላይ የነበረውን የትራፊክ መጨናነቅ መቅረፉ የሚያስችል ነውም ተብሏል።
የድልድዩ ግንባታ ተቋራጭ የቻይናው ኮሙዩኒኬሽን ኮንስትራክሽን ኩባንያ CCCC ሲሆን ግንባታውን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ እየሠራ መሆኑን ገልጿል።
አዲሱ የዓባይ ወንዝ ድልድይ በፊታችን በበጀት ዓመቱ መጨረሻ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል ተብሎም ይጠበቃል።
በጉብኝቱ ላይ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማኅበራዊ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ስዩም መኮንን፣የኦሮሚያ የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊና የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ አባል ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ.ር) ፣ የአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ጋሻው አወቀ (ዶ.ር) እና ሌሎች የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ዘገባው የአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ነው።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!