
ባሕር ዳር: ሰኔ 10/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ” ነገን ዛሬ እንትከል ” በሚል ሀሰብ ሁለተኛው ምዕራፍ አረንጓዴ አሻራ በሀገር አቀፍ ደረጃ መጀመሩ ይታወሳል። በአማራ ክልልም ሁለተኛ ምዕራፍ የአረንጓዴ አሻራ የመጀመሪያ ዙር ተጀምሯል።
የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ኃይለማርያም ከፍያለው (ዶ.ር) በአማራ ክልል ባለፉት ዓመታት 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኖች ተዘጋጅተው 6 ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን ገልፀዋል። በአማራ ክልል ከነበረው 14 በመቶ የደን ሽፋን ወደ 16 በመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉንም ገልፀዋል። ችግኝ ተካለው ዘርፈ ብዙ ጥቅም ይዞ ማምጣቱንም ተናግረዋል።ባለፉት ዓመታት የየተከለው ችግኝ 7 መቶ ሺህ ሄክታር መሬት የሚሸፍን ነውም ብለዋል። የችግኝ ተከላው በከፍተኛ የሆነ የአፋር መከላትን መቀነስ መቻሉንም ገልፀዋል። የሥራ እድል መፍጠር መቻሉንም ገልፀዋል።
በአማራ ክልል ባለፉት ዓመታት 6 ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ አስታውቋል።
ባለፉት ዓመታት ከተተከሉት ችግኞች መካከል 25 በመቶ የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውንም ገልፀዋል።
በሁለተኛው ምዕራፍ የመጀመሪያ ዙር የችግኝ ተከላ 1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ችግኞች መዘጋጀታቸውንም ገልፀዋል። 1 ነጥብ 6 ቢሊዮን ችግኞች ይተከላሉም ብለዋል።
በምክትል ርእሰ መስተዳድር ማዕረግ የማኅበራዊ ክላስተር አስተባባሪ ስዩም መኮንን፤ ተግዳሮቾችን ለመጋፈጥ የችግኝ ተከላ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የችግኝ ተከላው ባለፉት ዓመታት በአማራ ክልል በተሠራው ሥራ አበረታች ለውጦች መታየታቸውንም አስታውቀዋል። በሁለተኛው ምእራፍም በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ይቀጥላል ነው ያሉት። የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በሚደረገው ትግል የበኩላቸውን እንዲወጡም ጠይቀዋል።
ዘጋቢ፦ታርቆ ክንዴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!