
ባሕር ዳር: ሰኔ 08/2015 ዓ.ም (አሚኮ) አለርት ኮምፕሬሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በቀን ለ30 ህጻናት አገልግሎት መስጠት የሚያስችል የህጻናት ዓይን ህክምና ማዕከል ለመገንባት በዛሬው ዕለት የመሰረት ድንጋይ ተቀመጠ። የህጻናት ዓይን ህክምና ማዕከል ግንባታ ማስጀመሪያ መርኃ ግብር ላይ በአለርት ሆስፒታል የአይን ህክምና ክፍል ኃላፊ ዶክተር ሰለሞን ቡሳ እንደገለጹት፤ ማዕከሉ በሀገሪቱ ያለውን የህጻናት ዓይን ህክምና ማዕከል ተደራሽነት ማስፋት የሚያስችልና በቀን ለ30 ህጻናት አገልግሎት የሚሰጥ ነው ብለዋል።
የግንባታው ወጪ 60 ሚሊየን ብር መሆኑን የጠቆሙት ዶክተር ሰለሞን፤ ክርስቲያን ብላይንድ ሚሸን (ሲቢኤም) የተባለው የጀርመን ተራድኦ ድርጅት ሙሉ በሙሉ ወጪውን እንደሚሸፋን አስታውቀዋል። ግንባታውን በሚቀጥለው ሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ዕቅድ መያዙንም ገልጸዋል። እንደ ኢፕድ ዘገባ ግንባታው ሲጠናቀቅ በቀን ለ30 ህጻናት አገልግሎት ከመስጠት በተጨማሪ ተኝቶ ማከም የሚያስችሉ ክፍሎች፣ የህጻናት ማቆያና ሌሎችም አገልግሎቶች ይኖሩታል ብለዋል። የጤና ሚኒስቴር የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ህይዎት ሰለሞን፣ የሲቢኤም ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!