
አዲስ አበባ : ግንቦት 25/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጂታል ነዳጅ ግብይትን አስመልክቶ ለተጠቃሚዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ በአዲስ አበባ አዘጋጅቷል።
በመድረኩ የተገኙት ተጠቃሚዎችና የነዳጅ ማደያ ሠራተኞች እንዳሉት ሲቢኢ ብር ዲጂታል የነዳጅ ግብይት ጊዜ ቆጣቢና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ያስቻለ ስለመኾኑ ገልጸዋል። በመድረኩ የነዳጅ ግብይት በቴክኖሎጅ እንዲፈጸም እየተሠራ ባለው ሥራ ውጤት እየተገኘበት መኾኑም ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሚዴቅሳ ቶሎሳ ባንኩ በመላ ሀገሪቱ ካሉ ከ1 ሺህ 100 በላይ የነዳጅ ማደያዎች ጋር በቅንጅት እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ በዲጂታል የነዳጅ ግብይቱ ዙሪያ በተጠቃሚው ዘንድ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለመፍታት የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኩ መዘጋጀቱን አስታውቀዋል።
ዲጂታል ግብይቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ እስከአሁን ከ8 መቶ 50 ቢሊዮን ብር በላይ በዲጂታል ግብይት መደረጉን የገለጹት ምክትል ፕሬዝዳንቱ ፤ የዲጂታል ነዳጅ ግብይቱ ለተጠቃሚው ኀብረተሰብ ቀልጣፋ አገልግሎት ከመስጠቱ በተጨማሪ በከፍተኛ የውጪ ምንዛሪ የሚገባው ነዳጅ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል እያስቻለ ነው ብለዋል።
ዘጋቢ፡- ሄለን ሃፍቴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!