
👉ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የመመሰጋገኛ እና የመደናነቅ ቀን እየተከበረ ነው።
አዲስ አበባ : ግንቦት 25/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በትምህርት ሚኒስቴር እና በቅን ኢትዮጵያ አማካኝነት “ተማሪ ለሀገር ሰላም” በሚል መሪ መልዕክት ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የመመሰጋገኛና የመደናነቅ ቀን በሚሊኒየም አዳራሽ እየተከበረ ይገኛል።
በዓሉ ለ3ኛ ጊዜ ምሥጋናና መደናነቅን ባሕል ለማድረግ ታስቦ ነው እየተከበረ ያለው።
በሥነ ሥርዓቱ ላይ የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ፋንታ ማንደፍሮ (ዶ.ር)፣ የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መስፍን (ዶ.ር)፣ የቅን ኢትዮጵያ መሥራች ቶሎሳ ጉዲና (ዶ.ር)፣ የተለያዩ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሲቪክ ማኅበራትና ልዩ ልዩ ተቋማት፣ በአዲስ አበባ ከሚገኙ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ተማሪዎችና መምህራን እንዲሁም ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ባለውለታዎቿን የማትረሳና ውለታ መመለስ የምትችል ሀገር ናት ያሉት ፋንታ ማንደፍሮ (ዶ.ር) ቅንነት፣ አመስጋኝነት እና መደናነቅን ከትምህርት ቤት መጀመር አለብን ብለዋል።
ወላጆች፣ መምህራን እና ተማሪዎች አመስጋኝ ትውልድ ለመፍጠር ትምህርት ሚኒስቴር ለሚያደርጋቸው መሠል የትምህርት ጥራት ንቅናቄዎች ድጋፍ እንዲያደርጉ ዶክተር ፋንታ ጠይቀዋል።
ሚኒስትር ዴኤታው ቅን ኢትዮጵያዊያንን እና መምህራንን አመሥግነዋል።
ዘጋቢ፡- ድልነሳ መንግሥቴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!