
ባሕር ዳር ፡ ግንቦት 08/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን በቤላሩስ የኢትዮጵያ የክብር ቆንስል የሆኑትን ሚስተር ዲሚትሪ ሉካሼንኮን በዛሬው ዕለት በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
የክብር ቆንስሉ በምሥራቅ አውሮፓዊቷ ሀገር ኢትዮጵያን እና ሕዝቧን በመወከል እያበረከቱት ስላለው አስተዋጽኦ አቶ ደመቀ ምስጋና አቅርበዋል።
“እርስዎ አምባሳደራችን ነዎት” በማለትም አድናቆታቸውን ገልጸውላቸዋል።
ኢትዮያ እና ቤላሩስ በተለይ በኢንቨስትመንት፣ ቱሪዝም፣ ግብርና ሜካናይዜሽን እና ማዕድን ዘርፎች የሁለትዮሽ ትብብራቸውን ይበልጥ ማጠናከር ይገባቸዋል ብለዋል አቶ ደመቀ።
“ይህን ለማሳካት በእኛ በኩል የምንችለውን እናደርጋለን” ብለዋል።
ሚስተር ዲሚትሪ ሉካሼንኮ በበኩላቸው በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ያላቸውን ቁርጠኝነት መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!