
አዲስ አበባ : ግንቦት 05/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን የተለያዩ የፈጠራ ቴክኖሎጂን ባበረከቱትና የዳግማዊ አፄ ምኒልክን የአንኮበር ቤተ-መንግሥት በማደስ ለቱሪዝም አገልግሎት እንዲውል ያደረጉትን ኢንጂነር ተረፈ ራሥ ወርቅ 1ኛ የሙት ዓመት መታሰቢያን ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀ መርሐ ግብር በሳይንስ ሙዚየም እየተከናወነ ነው።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በሰጠቻቸው የዕውቅናና የክብር ማዕረግ ጠቢበ ጠቢባን ኢንጂነር ተረፈ ራሥወርቅ 1ኛ የሙት ዓመት መታሰቢያ መርሐ ግብር ላይ የተለያዩ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ፣የሃይማኖት አባቶች፣ የሚዲያ ባለሙያዎች ፣ ባለቤታቸው ወይዘሮ ብርሃኔ አስፋውና ልጃቸው ኢንጂነር አንድነት ተረፈ ራስወርቅ እና ሌሎች ልጆቻቸውን ጨምሮ የውጭ ሀገር ዜጎችና ወዳጆቻቸው በተገኙበት እየታሰበ ነው።
በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ ባለሙያ የነበሩት በተለይም ከ60 ዓመት በፊት በኢትዮጵያ ፊደል የሚሠራ የቴሌክስ መኪና /ቴሌ ፕሪንተርን / ጨምሮ በርካታ የቴክኖሎጂ ፈጠራን ያበረከቱት ኢንጅነር ተረፈ ራሥወርቅ አበርክቷቸውንና ለቴክኖሎጂ ያላቸውን ፍቅር በማሰብ የፈጠራ ውጤቶችን ለመሸለምና በስማቸው ፋውንዴሽን በማቋቋም በዘርፉ የሚመጡ ወጣቶችን ዕውቅና ለመሥጠት የታሰበ ነው ተብሏል።
ዘጋቢ:-ድልነሳ መንግስቴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
