
ባሕር ዳር: ግንቦት 03/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ የቴክኖሎጂ ትራንስፎርሜሽንን ለማምጣት እየሠራች መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ.ር) ገልጸዋል፡፡
የአፍሪካ የግብርና ቴክኖሎጂ ፋውንዴሽን የአምስት ዓመት ስትራቴጂ ማስጀመሪያ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ ተካሂዷል።
በመርኃ ግብሩ መልእክት ያስተላለፉት ዶክተር በለጠ ሞላ የአፍሪካ ቴክኖሎጂ ፋውንዴሽን የአምስት ዓመታት (2023-2027) ስትራቴጂውን በኢትዮጵያ ማስጀመሩ ልዩ ትርጉም አለው ብለዋል።
ስትራቴጂው የአፍሪካን እድገትና ልማት በቴክኖሎጂ ለማረጋገጥ ከፍተኛ ቁርጠኝነት ያለው በመሆኑ ለተፈጻሚነቱና በዜጎች ላይ ትራንስፎርሜሽን ለማምጣት መነሳሳት ፈጥሮልናል ነው ያሉት፡፡
ሚኒስቴሩ ከኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት እና ከአፍሪካ ቴክኖሎጂ ፋውንዴሽን ጋር በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በቴክኖሎጂ መስክ የተወጠኑ አንዳንድ ሃሳቦችን ለመተግበር፣ አፍሪካ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ እና ፈጠራ ላይ ኢንቨስት ማድረግ እንደምትችል ማሳየት አለብን ማለታቸውንም የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!