
ገንዳ ውኃ: ሚያዝያ 23/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በሱዳን በተፈጠረው የእርስ በርስ ጦርነት የ42 ሀገራት ዜጎች በምዕራብ ጎንደር መተማ በኩል ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን የምዕራብ ጎንደር ዞን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን መምሪያ ገልጿል።
የመምሪያው ኀላፊ አቶ ፈንታሁን ቢሆነኝ እንዳሉት በሱዳን በተፈጠረው የእርስ በርስ ግጭት ጋር ተያይዞ ዞኑ ወደ አካባቢው ሊገባ የሚችለውን ተፈናቃይ ለመቀበል በሚቻልበት ጉዳይ ቅድመ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቷል።
እስከ ሚያዝያ 20/2015 ዓ.ም ባለው ጊዜ ብቻ ከ6 ሺህ በላይ የ42 ሀገራት ዜጎች መግባታቸውን ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥ ደግሞ 941 ኢትዮጵያውያን ናቸው። ተፈናቃዮቹ የጤና ችግር እንዳይገጥማቸው የጤና ባለሙያ በመመደብ አገልግሎት እየተሰጠ መኾኑንም ነግረውናል።
በዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት በኩል መካከለኛና ከፍተኛ ተሽከርካሪዎች ተመድቦ ተፈናቃዮች ወደ የሚፈልጉት አካባቢ የመሸኘት ሥራ ተሠርቷል። የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበርም ውኃና ብስኩት በማቅረብ እያገዙ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
በቀጣይ ችግሩ እየሰፋ የሚሄድ ከኾነ ወደ ቀጣናው ሊገባ የሚችለውን ስደተኛ ሊያስተናግድ የሚችል ቦታ የመለየት ሥራ ተሠርቷል ብለዋል።
ዘጋቢ፦ ዳግማዊ ተሠራ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!