
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 19/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢትዮጵያ የታሪክ ባለሙያዎች ማኅበር” ትስስርና መስተጋብር በኢትዮጵያ ታሪክ” በሚል ርዕስ ያሳተመውን መጽሐፍ ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አበረከተ፡፡
የማኅበሩ ተወካይ ኤምሬተስ ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ መጽሃፍቱን ለኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ አስረክበዋል፡፡
የታሪክ ኤምሬተስ ፕሮፌሰር ባህሩ የማኅበሩ መቋቋም ዋና ዓላማ ማኅበረሰቡ ትክክለኛ የታሪክ አረዳድን እንዲያውቅ እና ታሪክ የመፍትሄ አካል እንዲሆን ለማስቻል ነው ብለዋል፡፡
በሌላ መልኩ ታሪክ ለሀገራዊ መግባባት ትልቅ ሚና መጫወት እንደሚችል ማስረዳትም የማኅበሩ ዓላማ መሆኑን ጠቅሰዋል።
መጽሐፉ የ18 የጥናት ጽሁፎችን ሃሳብ መያዙ የተገለጸ ሲሆን ኮሚሽኑ በቀጣይ ለሚያከናውናቸው ሥራዎች ከታሪክ አንጻር ያሉ እውነታዎችን ለመረዳት አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ ከማኅበሩ የተረከቡት መጽሃፍ ለኮሚሽኑ ሥራዎች አጋዥ መሆኑን ጠቅሰው ምስጋና አቅርበዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!