
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 15/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በሰላም የምትታወቀው ኢትዮጵያ ከነበረችበት አስከፊ ጦርነት ወጥታ በሰላም ጎዳና እንድትራመድ ለማድረግ የተደረገው ጥረት እና የተሄደበት መንገድ ውጤታማ እንደነበር በአዲስ አበባ በወዳጅነት አደባባይ ‘
ጦርነት ይብቃ፤ ሰላምን እናጽና’ በሚል መሪ ሐሳብ የምስጋና እና የዕውቅና ሥነ ስርዓት ላይ የተገኙት የቀድሞ የናይጀሪያ ፕሬዚዳንትና የአፍሪካ ሕብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ኦሊሴንጎን ኦባሳንጆ ተናግረዋል።
ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ በኢፌዴሪ መንግሥት እና በህወሓት መካከል የነበረውን ግጭት ለመፍታት ብዙ ጥረት መደረጉን ገልጸው ውጤት በመምጣቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል።
ኦሊሴንጎን ኦባሳንጆ “ለዚህ የሰላም ማስፈን ሥራ ስሰለፍ ጦርነቱ ቆሞ ሰላም እንደሚፈጠር ሙሉ ተስፋ ነበረኝ” ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ መንግሥትም ሆነ በህወሓት በኩል ለሰላም የነበረው ቁርጠኝነት አሁን ለመጣው ሰላም እንዳገዘ አስረድተዋል።
የሰላም ሂደቱን ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግሥት ስምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግ ያሳየውን ቁርጠኝነት አድንቀዋል።
በጦርነቱ ህይወት መጥፋቱ እንዳሳዘናቸው የተናገሩት ኦሊሴንጎን ኦባሳንጆ አሁን በተገኘው ሰላምም ደስታቸውን ገልጸዋል፡፡
በምሥጋናው ብርሃኔ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!