
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 15/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵያን የመልሶ ማቋቋም ሥራዎች ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗን የደቡብ አፍሪካ የዓለም አቀፍ ግንኙነት እና ትብብር ሚኒስትር ናሌዲ ፓንዶር ገለፁ።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከደቡብ አፍሪካ የዓለም አቀፍ ግንኙነት እና ትብብር ሚኒስትር ናሌዲ ፓንዶር ጋር በፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት አተገባበር ዙሪያ ተወያይተዋል።
አቶ ደመቀ፤ የሰላም ስምምነቱ በተገቢው መንገድ እንዲሄድ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ላደረገው ድጋፍ አመስግነው፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ስምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑን ገልፀዋል።
በኢትዮጵያ በጦርነት ጉዳት የደረሰባቸው አካባቢዎችን መልሶ ለማልማት እና ነዋሪዎችን ለማቋቋም የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
ሚኒስትር ናሌዲ ፓንዶር ደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵያ የሰላም ሂደት አካል በመሆኗ ኩራት እንደሚሰማቸው ገልፀው፤ የሰላም ስምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግ ሀገራቸው ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል።
ለአፍሪካ ችግሮች የአፍሪካ መፍትሄዎች በመስጠት ግጭቶችን ከመፍታት ባለፈ በመልሶ ግንባታ እና በመልሶ ማቋቋም ሥራዎች ላይ ትኩረት መስጠት እንደሚያስፈልግ መናገራቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ሚኒስትሯ ደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵያ የመልሶ ማቋቋም ሥራዎችን በተለይም በትምህርት ዘርፍ ላይ ለማገዝ ፍላጎት እንዳላት ገልጸዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!