
“ዘካተል ፊጥር ከዒድ በፊት የሚከወን አቅመ ደካሞች በዓሉን በደስታ እንዲያሳልፉ የሚሰጥ ስጦታ ነው” የአፋር ክልል የቀድሞ ሸሪዓ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 12/2015 ዓ.ም (አሚኮ)ዘካተል ፊጥር ከረመዷን ፆም መጠናቀቅ ጋር በተያያዘ ሃይማኖታዊ ግዴታ የሆነ የዘካ አይነት እንደሆነ የእስልምና አስተምሮ ያስረዳል።
ዘካ ለድሆች በዒድ እለት ሰዎችን ከመለመን እንዲድኑ፣ የእለቱ ደስታ ተካፋይ እንዲሆኑና በፆም ወቅት ተከስተው ላለፉ አንዳንድ ጉድለቶች ማሟያ እንዲሆን ተብሎ የተደነገገ አስተምሮም እንደሆነ የሃይማኖት አባቶች ይናገራሉ።
ከአሚኮ ጋር ቆይታ ያደረጉት የአፋር ክልል የቀድሞ ሸሪዓ ምክርቤት ፕሬዚዳንት ሼህ ደረሳ ሙሐመድ ዘካተል ፊጥርን ከሌሎች ዘካ አይነቶች ለየት የሚያደርገው ከኢድ በኋላ ሙስሊሙ ደስ ብሎት እንዲያከብር ሁሉም ሰው የሚረባረብበት በጎ ዓላማ ያለው ተግባር ነው ብለዋል፡፡
ዘካተል ፊጥር ማውጣት ግዴታ በሚሆንበት ቀን እና ሌሊት፤ ለራሱ እና ለቤተሰቦቹ የሚበቃ ያለው እንጂ ዘካትል ፊጥርን ለመስጠት የግድ የተትረፈረፈ ሃብት ሊኖረን አይጠበቅም ሲሉ ሼህ ደረሳ ሙሐመድ ገልጸዋል፡፡
ዘካተል ፊጥርን ከዒድ ሰላት በኋላ ማዘግየት የተከለከለና፤ መስጠት የሚጀመረውም ከረመዳን የመጨረሻው እለት ፀሐይ ከጠለቀችበት ወይም ዒድ መሆኑ ከተረጋገጠበት ሰዓት ጀምሮ እንደሆነ ሼህ ደረሳ ተናገረዋል።
የዒድ አልፈጥር እና የዘካተል ፊጥር ግንኙነት በዚህ ልክ እንዲሆን የተደረገውም ሰዎች ከኢድ በፊት በሚሰጣቸው ስጦታ በዓሉን በደስታ እንዲያሳልፉ ለማድረግ እንደሆነም ተመላክቷል።
ዘጋቢ፡- ሳሙኤል ኪሮስ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!