
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 04/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል መንግሥት ከዚህ በፊት በግላቸው ታጥቀው ሲንቀሳቀሱ የቆዩ ግለሰቦችን እና ቡድኖችን በማወያየት ወደ መደበኛ የጸጥታ አደረጃጀት እንዲገቡ ወይም ደግሞ ወደ መደበኛ ህይወታቸው እንዲመለሱ ጥረት ሲያደርግ መቆየቱ ይታወሳል።
በዚህ ጥረቱም በርካታዎች ጥሪውን ተቀብለው ተግባራዊ አድርገዋል። ነገር ግን በቅርቡ በሰሜን ወሎ ዞን አካባቢ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች የመንግሥትን ጥሪ ባለመቀበል ከመከላከያ ጋር ወደ ግጭት የገቡ መሆኑም ይታወሳል።
ሆኖም በቅርቡ የፋኖ አባላቱ ይፋዊ ይቅርታ በመጠየቅ የመንግሥትን የሰላም ጥሪ መቀበላቸውን በማሳወቅ ከክልሉ መንግሥት እና ከመከላከያ ሠራዊት አመራሮች ጋር ውይይት አድርገው ወደ መደበኛ ህይወት ለመመለስ መስማማታቸውን የክልሉ መንግሥት አስታውቋል።