
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 02/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በኢትዮጵያ ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የሕዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ያለመ ሦስተኛው ምእራፍ የምግብ ሥርዓት ማጠናከሪያ መርኃ ግብር በዚህ ዓመት ጥር ወር ጀምሮ ተግባራዊ መደረግ ጀምሯል።
የአማራ ክልል የምግብ ሥርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ሥራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብርም በባሕርዳር ይፋ ሆኗል።
የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኀላፊ
ኀይለማርያም ከፍያለው (ዶ.ር) እንዳሉት የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተለያዩ የልማት መርኃ ግብሮች ተግባራዊ እየተደረጉ ይገኛሉ።
ከነዚህ መካከል አንዱ የኢትዮጵያ የምግብ ሥርዓት መርኃ ግብር መሆኑን ያነሱት ቢሮ ኀላፊው ለሚቀጥሉት 7 ዓመታት ተግባራዊ እንደሚደረግ ነው ያስታወቁት።
በክልሉ በ9 ዞኖችና በ48 ወረዳዎች የሚተገበረው የምግብ ሥርዓት ማጠናከሪያ መርኃ ግብር 7 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሕዝብን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
የምግብ ሥርዓት ማጠናከሪያ መርኃ ግብር አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ሲሆን 5 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር እንደተመደበለትም ዶክተር ኀይለማርያም ገልጸዋል።
ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የሕዝቡን የምግብ ዋስትና ክፍተት ለመሙላት በየደረጃው የተዋቀረው አስፈጻሚ አካል በቁርጠኝነት መሥራት እንዳለበትም አሳስበዋል።
ዘጋቢ:–ስማቸው እሸቴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!