
ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 27/2012 ዓ.ም (አብመድ) “የሕግ የበላይነትን ለማስጠበቅ ከእኛ ምን ይጠበቃል?” በሚል ርዕሰ የሚመክር መድረክ በባሕር ዳር ከተማ ክልል ምክር ቤት አዳራሽ እየተካሄደ ነው።
የውይይቱ ዓላማም የሕግ የበላይነትን ለማስጠበቅ ከአያንዳንዱ ዜጋ ምን ይጠበቃል በሚል ጉዳይ ላይ በመምከር በክልሉ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ማድረግ ነው። መድረኩን ያዘጋጁት የአማራ ክልል ምክር ቤት እና የክልሉ የምሁራን መማክርት ጉባኤ በጋራ በመሆን ነው።
የአማራ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ወርቀሰሙ ማሞ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር “ውይይቱ ለተከበረው የአማራ ሕዝብ አስተዋእጾ ለማበርከት የምንመክርበት ነው” ብለዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎችም የሕግ የበላይነትን በማስከበር ረገድ የድርሻቸውን እንዲወጡ መልዕክት አስተልፈዋል። ሠላም የሁሉም ነገር መሠረት መሆኑን የተናገሩት አፈ ጉባኤዋ ሁሉም አካል ከቤቱ ጀምሮ የሕግ የበላይነትን የማስከበር ኃላፊነት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።
በመድረኩ በምሁራን አማካኝነት የውይይት መነሻ ሐሳብ ቀርቦ በተሳታፊዎች ውይይት የሚደረግበት ይሆናል።
ዘጋቢ፦ ደጀኔ በቀለ