እንሳሮ እና መርሀቤቴ ወረዳዎችን የሚያገናኘው የጀማ ድልድይ በመሰበሩ የትራንስፖርት አገልግሎት መቋረጡን የመርሀቤቴ ወረዳ መንገድ ትራንስፖርት ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።

312
ደብረ ብርሃን: መጋቢት 27/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በሰሜን ሸዋ ዞን የእንሳሮ እና መርሀቤቴ ወረዳዎችን የሚያገናኘው የጀማ ድልድይ ዛሬ በመሰበሩ መንገዱ ለተሽከርካሪ ዝግ ሆኗል። ይህ መንገድ ከአዲስ አበባ በሚዳ መርሀቤቴ በኩል እስከ ደሴ ድረስ የሚወስድ በአስፋልት ግንባታ ላይ የሚገኝ መንገድ ነው።
ከደብረ ብርሃን ወደ መርሀቤቴ ሚዳና ወረኢሉ ለመጓዝም የሚያገለግለው መንገድም ይህ መስመር ነው።
ዛሬ የመሰበር አደጋ የደረሰበት የጀማ ድልድይ ለረጅም ጊዜያት ጥገና ያልተደረገለትና በርካታ ተሽከርካሪዎችን ሲያሰተናግድ የቆየ ነው።
100 ሜትር ርዝመት ያለው የጀማ ድልድይ የቻይና ኮንስትራክሽን ኩባንያ የሆኑ ሁለት ሲኖትራክ ተሽከርካሪዎች በተመሳሳይ ጊዜ በድልድዩ ገብተው እየተጓዙ በነበረበት ወቅት ነው የመሰበር አደጋ ደርሶበታል የተባለው።
የመርሀቤቴ ወረዳ መንገድ ትራንስፖርት ጽሕፈት ቤት ኀላፊ በቂነው ስለሺ ድልድዩ በአንድ ጊዜ አንድ ተሽከርካሪን ብቻ ማሳለፍ የሚችል ቢሆንም ባልተለመደ ሁኔታ ሁለቱ ተሽከርካሪዎች እንደጫኑ ወደ ድልድዩ በመግባታቸው የመሰበር አደጋው ተከስቷል ብለዋል።
ለጊዜው መንገዱ ለተሽከርካሪ ቢዘጋም መጭው የትንሣዔ በዓል በርካታ ተሽከርካሪዎች የሚተላለፉበት በመሆኑ አስቸኳይ ጥገና እንዲሠራለት የማሳወቅ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል።
ጊዜያዊ ተለዋጭ መንገድ ለማዘጋጀት ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
ዘጋቢ:–ዮሐንስ ንጉስ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous article“የተፈጠረውን የኑሮ ውድነት ለማስተካከል መንግሥት የማስፈጸም አቅሙን ተጠቅሞ የንግድ ሥርዓቱን መቆጣጠር እና ማስተካከል ይጠበቅበታል” የምጣኔ ሃብት ባለሙያ አብዮት አልማው (ዶ.ር )
Next article“ዘመናዊ የመስኖ ልማት አውታሮችን በማስፋፋት የክልሉን አርሶ አደሮች የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሠራ ነው”