የምርጫ ሕጉን እና የፖለቲካ ፓሪቲዎችን የምዝገባ አዋጅ በመቃወም ሊደረግ የነበረው የርሃብ አድማ ላልተረወሰነ ጊዜ መራዘሙ ተገለጸ፡፡

141

የመኢአድ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የከ70 በላይ የፖለቲካ ፓርቲዎችን የወከለው አስተባባሪ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ሙሉጌታ አበበ እና የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ሕብረት ምክትል ሊቀ መንበር እና የኮሚቴው አስፈጻሚ አባል አቶ ገብሩ በርሄ በስልክ እንደተናገሩት 71 የሚሆኑ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከምርጫ እና ከፓርቲዎች ምዝገባ ሕጉ ውስጥ የሚሻሻሉ እና የሚሰረዙ ያሏቸው አንቀጾች ተለይተዋል፡፡
አዋጁ ማስተካከያ እስኪደረግበት ጊዜ ድረስም በሥራ ላይ እንዳይውሉ ለሚመለከተው የመንግሥት አካል በደብዳቤ ማሳወቃቸውንም ተናግረዋል፡፡ እንደ አቶ ሙሉጌታ እና አቶ አቶ ገብሩ ገለጻ ከትናንት ጥቅምት 25/2011 ዓ.ም ከሰዓት ጀምሮ ለ48 ሰዓት ሊደረግ የነበረው የርሃብ አድማ ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል፡፡
የርሃብ አድማው የተራዘመው ከከተማ አስተዳደሩ ይሁንታ ባለማግኘታቸው ምክንያት መሆኑንም ነው የተናገሩት፡፡ ጥያቄ ካስገቡ ጊዜ ጀምሮ የፈቃድም ሆነ የክልከላ ደብዳቤ እንዳልተሰጣቸው አቶ ሙሉጌታ እና አቶ ገብሩ ተናግረዋል፡፡ የርሃብ አድማውን ለማስፈጸም የተመረጡት አስፈጻሚ ኮሚቴዎች በተደጋጋሚ ወደ ቢሮ ቢሄዱም የቢሮ ኃላፊዎች ባለመገኘታቸው ምላሽ አላገኙም፡፡ የርሃብ አድማ ለማድረግ የመረጡትን አራት ኪሎ አደባባይ በሌላ ቦታ እንዲቀይሩ ትዕዛዝ እንደተሰጣቸውም ገልጸዋል፤ ይሁን እንጂ አቋማቸው በመረጡት ቦታ እና ጊዜ ማካሄድ እንደነበርም ተናግረዋል፡፡
ለጊዜው በኦሮሚያ ክልል በተፈጠረ የሠላም መደፍረስ ጉዳት ለደረሰባቸው ሰዎች የደም ልገሳ እና የቁሳቁስ ድጋፍ እያደረጉ መሆኑንም ነው የተናገሩት፡፡ ‹‹የርሃብ አድማው ላልተወሰነ ጊዜ ቢራዘምም ቢሮክራሲውን ሰብረን እስከምንወጣ ድረስ የምንታገል ይሆናል›› በማለትም ተናግረዋል፡፡ እንደ አቶ ሙሉጌታ እና አቶ ገብሩ ገለጻ የርሃብ አድማው በሌላ ጊዜ የሚደረግ ይሆናል፤ ቀን ግን አልተቆረጠለትም፡፡
ዘጋቢ፡- ደጀኔ በቀለ

Previous articleየአማራ ክልል በሩብ ዓመቱ ለ600 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ሰጠ፡፡
Next articleወላጆችና መንግሥት ወጪ በመጋራት የመጻሕፍት ችግርን ሊቀርፉ እንደሚገባ ትምህርት ቢሮ ሐሳብ አቀረበ፡፡