“በሱዳን እና ደቡብ ሱዳን ድንበር አካባቢ የሚስተዋሉ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት ከሀገራቱ ጋር በቅንጅት እየተሠራ ነው” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ

109
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 19/2015 ዓ.ም (አሚኮ) በሱዳን እና ደቡብ ሱዳን ድንበር አካባቢ የሚስተዋሉ ግጭቶችን በሰላም እና ውይይት ለመፍታት ከሀገራቱ ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገልጸዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ እየሰጡ ነው፡፡
በማብራሪያቸውም በሱዳን እና ደቡብ ሱዳን፣ የኢትዮዮጵያን ድንበር አልፈው ገብተዋል በሚል ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስር ዐቢይ፤ ኢትዮጵያ እና ሱዳን ላለፉት 60 እና 70 ዓመታት የድንበር ይገባኛል ጥያቄዎች እና ውዝግቦች ያሉባቸው መኾኑን አስታውሰዋል፡፡
ይህም የሀገራቱ የድንበር ማካለል ሥራ ባለመሠራቱ የመጣ መኾኑን ነው የተናገሩት፡፡
ችግሩን ከሱዳን መንግስት ጋር በሰላም እና ውይይት ለመፍታትም የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን መቋቋሙን አንስተዋል፡፡
ይህም የድንበር ወሰኑን በማካለል በሀገራቱ መካከል ያለውን ችግር ለዘለቄታው ለመፍታት የሚያስችል መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡
ድንበሩ እስኪካለል ድረስ በሁለቱ ወገኖች ያሉ አርሶ አደሮች እንዳይጉላሉ የሚል የጋራ ስምምነት መኖሩን ጠቅሰዋል፡፡
ይሁን እንጂ በአፈጻጸም ደረጃ የሚስተዋሉ ክፍተቶች መኖራቸውን ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ያብራሩት፡፡
ጉዳዩን በውይይት እና በንግግር መፍታት ይበልጥ ጠቃሚ እንደሚሆም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡
ደቡብ ሱዳን በተመለከተም ፣ ሀገሪቱ የሰውን ሀገር ለመውረር የሚስችል ፍላጎትም ሆነ ቁመና የላትም ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ይሁን እንጂ በቅርቡ ድርቅ ገጥሞናል በሚል 20 ሺህ ከብቶችን እየነዱ ወደ ኢትየጵያ የገቡ የሀገሪቱ አርብቶ አደሮች መኖራቸውን ጠቅሰዋል፡፡
አርብቶ አደሮችን ለማነጋገር ተሞክሯል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፤ ይሁን እንጂ ድንበራችንን የሚያሰጋ ነገር አይፈጠርም ብለዋል፡፡
ችግሩን ከደቡብ ሱዳን መንግሥት ጋር በውይይት ለመፍታት ስምምነት ላይ መደረሱንም አስገንዝበዋል፡፡
ዘጋቢ፦ በመላኩ ገድፍ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous article“ለሠላም የምንሠራው የድህረ ግጭት አውድ ጫና ውስጥ ኾነን ነው” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር)
Next articleየፈተና ጥሪ ማስታወቂያ