
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 12/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የ1444ኛው ዓመተ ሒጅራ የረመዷን ፆም ማክሰኞ (ዛሬ) ጨረቃ ከታየች ረቡዕ (ነገ)፣ ካልኾነ ግን ሐሙስ (ከነገ በስቲያ) እንደሚጀምር የፌዴራል ጠቅላይ ሸሪዓ ፍርድ ቤት አስታወቀ።
ፍርድ ቤቱ የ1444ኛው ዓመተ ሒጅራ የረመዷን ፆምን ምክንያት በማድረግ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላልፏል።
“ለመላው ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እንኳን ለ1444ኛው ዓመተ ሒጅራ የረመዷን ጾም በሰላም አደረሳችሁ፤ ለዚህ የተከበረ ታላቅ ወር ረመዷን በሰላም ላደረሰን አላህ ምስጋና እናቀርባለን” ብሏል ፍርድ ቤቱ በላከው መግለጫ።
ሕዝበ ሙስሊሙ የተለመደ የእርስ በርስ መደጋገፍ እና መረዳዳት ተግባሩን በፆሙ ወቅት ይበልጥ አጠናክሮ እንዲቀጥልበት ፍርድ ቤቱ ጥሪ አቅርቧል።
ለመላው ኢትዮጵያውያን እና የዓለም ሙስሊሞች ወሩ የጤና፤ የሰላምና የፍቅር እንዲሆን ፍርድ ቤቱ መልካም ምኞቱን ገልጿል ሲል ኢቢሲ ዘግቧል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!