
ባሕርዳር: መጋቢት 11/2015 ዓ.ም (አሚኮ)በወጪ ንግድ ሥርዓቱ ላይ ባለው ክፍተት ከሀገሪቱ የተለያዩ ምርቶች በሕገ ወጥ መንገድ እንደሚወጡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ተናገሩ፡፡
የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ሀገራዊ የቅንጅት መድረክ በሸራተን አዲስ እየተካሄደ ነው፡፡
አቶ ደመቀ በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር “የተለያዩ ምርቶች በሕገ ወጥ መንገድ ከሀገር እየወጡ አንጡራ ሀብታችንን እያሳጡን ነው” ብለዋል፡፡
ባለፉት ዓመታት ከውጭ ኢንቨስትመንት ጋር ተያይዞ በተሠሩ ሥራዎች ለውጦች ቢኖሩም አሁንም ሥራዎች ያስፈልጋሉ ነው ያሉት።
ስለኾነም ሀገሪቱ አሁን ባለችበት ሁኔታ ሀገራዊ ኢኮኖሚውን ይበልጥ ለማነቃቃት ኢንቨስትመንቱን ማበረታታትና ሕገ ወጥነትን መግታት እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው ለዚህ ደግሞ ክልሎች ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ሊሠሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ሀገራዊ የቅንጅት መድረክ በ2003 ዓም በተደራጀ መልኩ ወደ ሥራ መግባቱ ይታወሳል።
እንደ ኤፍቢሲ ዘገባ በዛሬው ጉባኤ የውጭ ኢንቨስትመንት ሥርዓቱን ለማሳለጥ በተቋቋመው ብሔራዊ ኮሚቴ የተሠሩ ሥራዎች እንዲሁም የፀረ ኮንትሮባንድ ብሔራዊ ኮሚቴ ስራን መገምገም ላይ ትኩረት ይደረጋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!