“በሥግብግብ ነጋዴዎች እና ደላላዎች ወዳልተፈለገ መንገድ እየሄድን ያለበትን መንገድ ማስቆም ተገቢ ነው” አቶ ግርማ የሽጥላ

394
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 02/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ንግድ እና ገበያ ልማት ቢሮ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ውይይት እያደረገ ነው።
በውይይቱ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ አቶ ግርማ የሽጥላ፤ ሀገራችን ብሎም ክልላችን የሰው ልጆች በሚፈልጉት ጸጋ የተሞላች ብትኾንም በሥግብግብ ነጋዴዎች ወዳልተፈለገ መንገድ እየሄድንበት ያለው መንገድ ሊቆም ይገባል ብለዋል።
በኢትዮጵያ ይሁን በዓለም በቂ መሠረተ ልማት ባልነበረበት ዘመን የሲራራ ነጋዴ ከቦታ ቦታ ምርት በማዘዋወር ኀላፊነቱን ይወጣ እንደነበር አንስተዋል። አሁን ሳያመርት ገዝቶ ሳይገዛ ሸጦ ትርፍ የሚያገኝበት ዘመን ላይ ደርሰናል፤ ነገር ግን እየተፈጠረ ያለውን ምቹ ኹኔታ ወዳልተፈለገ መንገድ በመጠምዘዝ ሕገወጥነትን እንደ ሕጋዊነት ለመውሰድ የሚፍጨረጨር አካል መኖሩ የተፈጠረውን ጥሩ አጋጣሚ ወዳልኾነ መንገድ እየጠመዘዘው መኾኑን አንስተዋል።
May be an image of one or more people, people sitting and people standing
ይኽን ልናስቆምበት የምንችልበትን ሥርዓት ቢሮው ሊፈጥር እንደሚገባ አሳስበዋል።
ጤናማ የንግድ ሥርዓት በመዘርጋት አምራቹን፣ ሸማቹን እና ነጋዴውን እኩል ተጠቃሚ የሚያደርግ የንግድ ሥርዓት ሊዘረጋ እንደሚገባ አሳስበዋል። በገበያ ሥርዓት የሚመራ የንግድ እና ግብይት ሥርዓት መፈጠር አለበትም ብለዋል።
አምራቹ ማኅበረሰብን ተጠቃሚ የማያደርግ፣ ለሸማቹ የተጋነነ ዋጋ በማቅረብ የሚያማርሩ ነጋዴዎችን በመቆጣጠር ንግድ እና ገበያ ልማት ቢሮ እስከታች ካሉ ባለድርሻ አካላት ጋር ሊሠራ እንደሚገባም አሳስበዋል።
ዘጋቢ፦ ትርንጎ ይፍሩ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous article“የሠለጠነ የሰው ኀይል ለመፍጠር ሥንሠራ ገበያው የሚፈልገው ስለመኾኑ ትኩረት መስጠት ይገባል” ምክትል ርእሰ መሥተዳድር ጌታቸው ጀንበር (ዶ.ር)
Next articleየባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ 60ኛ ዓመትን አስመልክቶ የቀድሞ “ፖሊ እና ፔዳ” ተማሪዎች ኮንፈረንስ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው።