
የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት እና ከተማ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ
ባሕርዳር:የካቲት 30/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢንቨስትመንት መሬት ወስደው አጥረው የሚያስቀምጡ ባለሃብቶች ቁጥር መበራከቱ የክልሉን ኢኮኖሚ እየጎዳ መኾኑን የአማራ ክልል ምክር ቤት የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት እና ከተማ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገልጿል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ በላይ ዘለቀ የወሰዱትን መሬት በአግባቡ የሚያለሙ ባለሃብቶች ቢኖሩም አጥረው የሚያስቀምጡ መበራከታቸውን ለምክር ቤቱ ገልጸዋል።
የተከበሩ አቶ በላይ ለአልሚዎች የተላለፈ መሬት ግንባታው ተጠናቅቆ ወደ ማምረት መግባት ባለመቻሉ ለወጣቶች የሚፈጠረውን የሥራ ዕድል እያሳጣ ነው ብለዋል። ማምረት ባለመቻሉም የክልሉን ብሎም የሀገርን ኢኮኖሚ እየጎዳ ስለመኾኑ ተናግረዋል።
በቀጣይነት በየከተሞች ታጥረው የተቀመጡ የልማት ቦታዎች ወደ ሥራ እንዲገቡ ለማስቻል ቋሚ ኮሚቴው ከፈጻሚ አካሉ ጋር በመቀናጀት የክትትል እና ቁጥጥር ሥራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም የተከበሩ አቶ በላይ ዘለቀ ተናግረዋል።
ዘጋቢ:- አሚናዳብ አራጋው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!