
ጥቅምት 06/2015 ዓ.ም (አሚኮ) የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ የገነባውን የሰራዊት መኖሪያ ቤት መርቀው ከፍተዋል።
ሌተናል ጄኔራሉ የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ የአየር ኃይል አባላትን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ በአጭር ጊዜ ሠርቶ ያስረከበው ቤት የሚያስመሰግን መሆኑን ተናግረዋል።
በዕለቱም በመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ኃላፊ ተወካይ ብርጋዴር ጀኔራል ደረጄ መገርሳ የተመራ ሉዑክ በዋና መምሪያው ተገንብተው የተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን እና በግንባታ ሂደት ላይ የሚገኘውን የአየር ወለድ ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ጎብኝተዋል።
የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ኮንስትራክሽን መምሪያ የአየር ወለድ ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ፕሮጀክት ኃላፊ ኢንጅነር ሻለቃ ፍቃዱ ያዘው ፕሮጀክቱ የደረሰበትን ደረጃ ለልዑኩ ገለጻ አድርገዋል።
ከጉብኝቱም በኋላ የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ኃላፊ ተወካይ ብርጋዴር ጀኔራል ደረጄ መገርሳ የግንባታ ፕሮጀክቱ በተያዘለት የጊዜ ሠሌዳ በጥራት ተሠርቶ መጠናቀቅ እንደሚገባው መግለጻቸውን ከመከላከያ ሰራዊት የተገኘ መረጃ ያመላክታል።
ለሀገር ክብር በትግል እናብር‼