
አዲስ አበባ፡ ጥቅምት 04/2015 ዓ.ም (አሚኮ) 17ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን “ሕብረብሔራዊ አንድነት ለዘላቂ ሰላም” በሚል መሪ ቃል ይከበራል ሲሉ የፌደሬሽን ምክርቤት አፈጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ገልጸዋል።
የበዓሉ መከበር አላማ የኢትዮጵያን ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች አንድነትና አብሮ የመኖር ዕሴትን ለማጠናከር ጉልህ ሚና ይኖረዋልም ብለዋል።
የኢፌዴሪ ሕገመንግስት የፀደቀበትን ህዳር 29 የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን ተብሎ በየዓመቱ እንዲከበር የኢፌዴሪ የፌድሬሽን ምክርቤት በሚያዚያ 21 ቀን 1998 ዓ.ም መወሰኑ ይታወሳል።
የዘንድሮ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በሁሉም ክልሎች እንዲከበር የኢፌዴሪ የፌደሬሽን ምክርቤት ያስተባብራል ሲሉ የኢፌዴሪ የፌደሬሽን ምክርቤት አፈጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ገልፀዋል፤ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የሁሉም ማኅበረሰብ ኀላፊነት መሆኑ በማስገንዘብ።
አንድነትና የሕዝቦችን ትስስር ማጠናከርና ልዩነቶችን በማጥበብ ለሀገራዊ አንድነት የምንሰራበት ይሆናል ያሉት ደግሞ በፌዴሬሽን ምክርቤት ጽሕፈት ቤት የዲሞክራሲ ባህል ግንባታ ዳይሬክተር ትግሉ መለሰ ናቸው።
ሕብረ ብሔራዊ ፌደራላዊ ስረዓት የብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ራስን በራስ የማስተዳደር በቋንቋ የመናገር፣ የመፃፍ፣ ቋንቋን የማሳድግ ባህልን የመግለፅና የማዳበር የማስፋፋት ህገ መንግስታዊ መብቶችን ለማረጋገጥ የሚከበር መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የታለመለትን ዓላማ ማሳካት ባይችልም በዓሉ ሲከበር መቆየቱን ገልፀው፤ በኢፌዴሪ የፌደሬሽን ምክርቤት አስተባባሪነት በሲዳማ ክልል “ሕብረብሔራዊ አንድነት ለዘላቂ ሰላም” በሚል መሪቃል ይከበራል ሲል የኢፌዴሪ የፌደሬሽን ምክርቤት አስታውቋል ።
ዘጋቢ፦አየለ መስፍን
ለሀገር ክብር በትግል እናብር‼