“ግሸን ደብረ ግሸን ከርቤ ከእስክንድሪያ እስከ ኢትዮጵያ”

512

መስከረም 21/2015 ዓ.ም (አሚኮ) ዳግማዊ ኢየሩሳሌም፤ የሰማያዊቷ እና አዲሲቷ ኢየሩሳሌም መግቢያ በር፡፡ ተምሳሌትነቷ የመንግስተ ሰማያት አምሳል፤ ከፍታዋ የተራሮች ሁሉ አናት፡፡ የኢየሱስ ክርስቶስ ግማደ መስቀል ማደሪያ መስቀለኛ ቦታ ናት ግሸን ደብረ ከርቤ፡፡

አካባቢውን በጥንታዊቷ የኢትዮጵያ ታሪክ የመካከለኛው ዘመን የሃይማኖት፣ ፍልስፍና እና የሥነ መንግስት ምሰሶ አደርገው የሚወስዱትም አሉ፡፡

አይሁድ በቅናት እና በፍርሃት በጥልቅ የቀበሩትን ግማደ መስቀል የተራራዋ እመቤት በከፍታዋ ከፍ አድርጋ አስቀመጠችው፡፡ ግሸን ኢየሩሳሌምን ትመስላለች፤ ሰማያዊቷንም ዓለም ትወክላለች እንዲሉ፡፡ ዓለም ከጥፋቱ በሥራው ሳይሆን በምህረቱ ይድን ዘንድ ግሸን የታታሪ ነገስታት፣ የትጉ ካህናት እና የጹኑ መንግስታት ማደሪያ ሆነችላቸው፡፡ ግሸን ደብረ ከርቤ ከእስክንድሪያ እስከ ኢትዮጵያ የክርስትና መደላድል ሆነች፡፡

ፈቅዶላቸው ደጇን እና ብቸኛውን በሯን የረገጡ ሁሉ ደስታቸው ወሰን፤ ሃሴታቸው ልክ የለውም፡፡ በሯን ያልረገጡ ክርስቲያኖች ደግሞ “ውል ውል አለኝ ደጅሽ፤ የአምላክ ፈቃድ ሆኖ እስክሳለምሽ” እያሉ ምድራዊቷን እና ዳግማዊቷን ኢየሩሳሌም እንደ ሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም ሁሉ በተስፋ ይጠብቃሉ፡፡

ሃይማኖት ብቻ ሳይሆን ማንነትም የከተመባት ተራራ የመካከለኛው ዘመን የኢትዮጵያ ነገሥታት ካቆሟቸው ታላላቅ የፖለቲካ ተቋማት መካከል የግሽን አምባ አካባቢ አንዱ ነው፡፡ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር እና ርክክብ ሲባል በሞት ወይም በኀይል ከስልጣን የወረዱ ነገሥታት ልጆች እና የቅርብ ዘመዶች በግዞት ግሸን አምባ ላይ ይቀመጡ እንደ ነበር ታሪክ ይነግረናል፡፡

በኢትዮጵያ የሥነ መንግሥት እና የፖለቲካ ታሪክ የሰማያዊው ዓለም የሰላም ምንጭ የሆነችው ዳግማዊቷ ኢየሩሳሌም በምድርም እንዲህ የሰላም አምባ ሆና አገልግላለች፡፡

ከ1278 ዓ.ም ጀምሮ እና የአጼ ይኮኖ አምላክ እረፍትን ተከትሎ የግሸን አምባ አካባቢ እንደ አንድ የመንግሥት ተቋም ለብዙ ጊዜ አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ በሃይማኖትም በአምባው ላይ በተለያዩ ዘመናት እንደተገነቡ የሚነገርላቸው አምስት አብያተ ክርስቲያናት አሉ፡፡ የግሸን ማሪያም እና የእግዚያብሔር አብ አብያተ ክርስቲያናት መሰረታቸው የቆመው በአጼ ካሌብ ዘመነ ንግሥና እንደነበር ይነገራል፡፡

ግሸን ደብረ ከርቤ ስሟ የበዛ የመማጸኛ ተራራ ናት፡፡ ዘመን በተቀየር እና ተዓምር በተፈጠረ ሁሉ ስያሜዋም ሲቀያየር ቆይቷል፡፡ ዛሬም ድረስ የዓለም ክርስቲያኖች የኢትዮጵያ ወገኖች ወደ ተራራዋ እመቤት መስከረም 21 በየዓመቱ ይተምማሉ፡፡ የታደሉ ልቦች የበረቱ እግሮች ቀጭኗን መንገድ እና ብቸኛዋን ደጅ ይረግጣሉ፡፡

ከአጼ ካሌብ እስከ አጼ ዘርዐ ያዕቆብ የጥንታዊ ነገሥታት አሻራ ያረፈባት እና የክርስቶስ ፈቃድ የከተመባትን የሰላም ተራራ በፍቅር ሀገር ወሎ በወርሃ መስከረም መመልከት መታደልም፤ መመረጥም ነው፡፡ ግሸንን መጎብኘት ዘመናትን በጽናት፤ ዓመታትን በብርታት እስከ እሴቷ እና ማንነቷ የዘለቀችውን ኢትዮጵያን መጎብኘት ነው፡፡

በታዘብ አራጋው

ለሀገር ክብር በትግል እናብር!!

ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
ዩቱዩብ https://bit.ly/2RnNHCq
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ
ትዊተር https://bit.ly/336LQaS
ቲክቶክ https://bit.ly/32rKF5J

Previous articleየብፁዕ አቡነ በርናባስ ጥሪ…
Next articleበኩር ጋዜጣ – መስከረም 23/2015 ዓ.ም ዕትም