
ባሕር ዳር፡ ጥቅምት 10/2012 ዓ.ም (አብመድ) አምና በተመሳሳይ ወቅት ከተያዙት የ489 ሚሊዮን ብር ግምታዊ ዋጋ ብልጫ ያላቸው የኮንትሮባንድ እቃዎችን መያዙን የጉምሩክ ኮሚሽን ገለፀ፡፡
ኮሚሽኑ በያዝነው በጀት ዓመት በመጀመሪያው ሩብ ዓመት ግምታዊ ዋጋቸው 687 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር የሆኑ ገቢና ወጭ ኮንትሮባንድ እቃዎችን መያዙን አስታውቋል፡፡
የተያዙትም የጦር መሳሪያዎች፣ የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች፣ መድኃኒቶች፣ አደንዛዥ እፆች፣ ምግብ ነክ ሸቀጣ ሸቀጦች፣ ኤሌክትሮኒክስና ልዩ ልዩ መለዋዎጫ እቃዎች፣ ልባሽና አዳዲስ ጨርቆች፣ ወደ ሀገር እንዳይገቡ ክልከላና ገደብ የተደረገባቸው እቃዎች መሆናቸውን ነው ኮሚሽኑ የገለጸው፡፡
አምና በተመሳሳይ ወቅት ከተያዙት እቃዎች ጋር ሲነፃፀር የ489 ሚሊዮን ብር ግምታዊ ዋጋ ብልጫ እንዳላውም ታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ኮሚሽኑ በሩብ ዓመቱ ለመሰብሰብ ካቀደው 24 ነጥብ 84 ቢሊዮን ብር ገቢ 26 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ወይም የእቅዱን 107 በመቶ እንደሰበሰበ አስታውቋል፡፡
ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር አፈጻጸሙ ሲነጻጸርም የ8 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር ወይም የ44 በመቶ ብልጫ እንዳለው ተመላክቷል፡፡