
ባሕር ዳር፡ መስከረም 30/2012 ዓ/ም (አብመድ) በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶክተር) 100ኛው የኖቤል ሽልማት አሸናፊ መሆናቸውን በመስማቱ መደሰቱን ገልጿል፤ ለጠቅላይ ሚኒስትሩና ለኢትዮጵያ ሕዝብም ‹የእንኳን ደስ አላችሁ› መልዕክት አስተላልፏል፡፡
ኤምባሲው ‹‹ለሠላምና ዓለማቀፋዊ ጥምረት ባረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ እና ከኤርትራ ጋር የነበረውን የድንበር ቅራኔ ለመፍታት በሄዱት ርቀት›› አሸናፊ መሆናቸው እንዳስደሰተው ነው የገለጸው፡፡
ሽልማቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመሪነት ዘመናቸው እያስመዘገቡ ላለው ስኬት ማሳያ መሆኑንም ኤምባሲው አመልክቷል፡፡
የዴሞክራሲ መርሆዎችን ለመተግበር፣ አካታች ልማት ለማምጣት፣ የፖለቲካ ምኅዳሩን ለማስፋት፣ የመገናኛ ብዙኃን ነፃነትን ለማረጋገጥና እስረኞችን ለመፍታትና የምጣኔ ሀብት ሽግግር ለማምጣት ዶክተር ዐብይ ያሳዩትን ቁርጠኝነትም አድንቋል፡፡
አሜሪካ የኢትዮጵያን ሕዝብና መንግሥት በመደገፍ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትና ብልጽግና እንዲኖር እንደምትደግፍም ኤምባሲው አስታውቋል፡፡