
ባሕር ዳር፡ መስከረም 30/2012 ዓ/ም (አብመድ) የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ (ዶክተር) የኖቤል የሰላም ሽልማት አሸናፊ ሆኑ።
የ2019 የሠላም ኖቤል ሽልማት አሸናፊ ዛሬ ይፋ ሆኗል፤ የማሸነፍ ከፍተኛ ግምት ከተሰጣቸው አራት ዕጩዎቹ አንዱ የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶክተር) ማሸነፋቸውም ተረጋግጧል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል የነበረውን ለሁለት አስርት ዓመታት የዘለቀ ቅራኔ ወደ ሠላም በመመለስ፣ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ተቋማትን በመገንባትና በሱዳንና ደቡብ ሱዳን የነበሩ ችግሮች እንዲፈቱ ያደረጉት ጥረትና ያስመዘገቧቸው ስኬቶች ናቸው አሸናፊ ያደረጓቸው ተብሏል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሸናፊ በሆኑበት 100ኛው የኦስሎ የሠላም የኖቤል ሽልማት 301 ዕጩዎች ተካትተው ነበር፤ ከእነዚህ ውስጥ 223 ግለሰቦች ሲሆኑ 78 ደግሞ ተቋማት ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ዕጩዎች ሦስት ግለሰቦችና አንድ ተቋም ለመጨረሻ ዕጩ ሆነው ነበር፤ በውጤቱም ጠቅላይ ሚኒስት ዐብይ አሸናፊ ሆነዋል፡፡
ሽልማቱን በታኅሳስ ወር የሚቀበሉ መሆኑና የገንዘብ ሽልማቱም 900 ሺህ የአሜሪካ ዶላር እንደሚደርስ ቢቢሲ አስነብቧል፡፡